Meseret Media
Meseret Media
February 27, 2025 at 08:00 PM
በአዲስ አበባ ከተማ የአጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት በሽታ መከሰቱን የጤና ባለሙያዎች ጠቆሙ (መሠረት ሚድያ)- በመዲናዋ ውስጥ የአጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት (አተት) በሽታ እንደተከሰተ የጤና ባለሙያዎች ለሚድያችን በሰጡት ቃል አሳወቁ። የበሽታው መከሰትን ለመሠረት ሚድያ ያረጋገጡት እነዚህ በአዲስ አበባ ጤና ቢሮ ስር ባሉ ጤና ጣቢያ የሚሰሩ የጤና ባለሙያዎች ስጋቱ ለህዝብ ይፋ ሆኖ የጥንቃቄ እርምጃዎችን በተመለከተ መልዕክት አለመተላለፉ የበለጠ ጉዳት እንዳያስከትል ስጋታቸውን ገልፀዋል። "ሰሞኑ ከፍተኛ የአተት በሽታ ተከስቷል፣ ነገር ግን ምንም እየተባለ አይደለም። እኛም በየጤና ጣቢያ ሸራ ወጥራቹ ዝም ብላችሁ ስሩ እየተባልን ነው" ያለው አንድ የጤና ባለሙያ በአስደንጋጭ መልኩ 'vibrio cholerae' የተባለው የኮሌራ አምጪ ተህዋስም በምርመራ ወቅት በከተማው ውስጥ መገኘቱን ተናግሯል። "እንደምናውቀው አተትም ሆነ ኮሌራ በጣም ተላላፊ ነው፣ ነገር ግን እየሆነ ያለው ነገር ፍፁም ተቃራኒ ነው" የሚሉት የጤና ባለሙያዎቹ ከ100 በላይ የበሽታው ተጠቂዎች አሁን ላይ ባሻ ወልዴ ተብሎ በሚጠራው የአራዳ ክፍለ ከተማ ጤና ማዕከል ገብተው እንደሚገኙ አረጋግጠዋል። "አሁን በዚህ ሰአት በርካታ ታማሚዎችን ካለ በቂ መከላከያ እና መሸፈኛ እያከምን ነው፣ አስቸኳይ መፍትሄ እንሻለን" ያሉን ሌላኛው የጤና ባለሙያ ናቸው። ከሰሞኑ በጋምቤላ ክልል ኑዌር ብሔረሰብ ዞን አራት ወረዳዎች የአጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት በሽታ ተከስቶ የዘጠኝ ሰዎችን ሕይወት መንጠቁ ታውቋል። በዚህ ዙርያ ከጤና ሚኒስቴር ተጨማሪ መረጃ ለማግኘት በመሞከር ማብራርያ እናቀርባለን። ፎቶ: ፋይል መረጃን ከመሠረት!
Image from Meseret Media: በአዲስ አበባ ከተማ የአጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት በሽታ መከሰቱን የጤና ባለሙያዎች ጠቆሙ   (መሠረት ሚድያ)- በ...

Comments