
Ethiopian Human Rights Commission - ኢሰመኮ
June 10, 2025 at 09:15 AM
ሀገር አቀፍ ውይይት፦ የሰብአዊ መብቶች ክትትል፣ ምርመራ እና ስነዳ
...
የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ከፕሮጀክት ኤክስፔዳይት ጀስቲስ (Project Expedite Justice, PEJ) ጋር በመተባበር በሰብአዊ መብቶች ክትትል፣ ምርመራ እና ስነዳ ላይ ሀገር አቀፍ የውይይት መድረክ ግንቦት 25 ቀን 2017 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ከተማ አካሂዷል።
በኢሰመኮ፣ ሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች እና ሌሎች ባለድርሻዎች መካከል ያለውን ትብብርና ቅንጅት ማጠናከርን ዓላማ ባደረገው ውይይት በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር፣ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ፣ በሲዳማ እና በደቡብ ኢትዮጵያ ክልሎች በሰብአዊ መብቶች ላይ የሚሠሩ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች፣ መንግሥታዊ ያልሆኑ ተቋማት እና ነጻ የሕግ ድጋፍ አገልግሎት ሰጪ አካላት ተሳትፈዋል።
በውይይት መድረኩ ኢሰመኮን ጨምሮ የሦስት ተቋማት የሰብአዊ መብቶች ክትትል፣ ምርመራ እና ስነዳን የተመለከቱ ገለጻዎች፣ መልካም ተሞክሮዎች እና ተግዳሮቶች ቀርበዋል። በኢሰመኮ የሰብአዊ መብቶች ክትትል፣ ምርመራ እና ስነዳ ፅንሰ ሐሳባዊ ማብራሪያ፣ የሰብአዊ መብቶች ስነዳ ዐይነቶች፣ የስነዳ አስፈላጊነት፣ በሰብአዊ መብቶች ጥበቃ እና ማስፋፋት ላይ ኢሰመኮ እና የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች የሚጋሯቸው ጉዳዮች፣ በሰብአዊ መብቶች ክትትል እና ምርመራ መካከል ያለው ልዩነት እና አንድነት እንዲሁም ተግባራዊ ሊሆኑ የሚገቡ የሰብአዊ መብቶች መርሖች፣ የሰብአዊ መብቶች ክትትል፣ ምርመራ እና ስነዳ ወሰን (scope) እና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ገለጻ ተድርጓል።
🔗 https://ehrc.org/?p=33387
#ethiopia🇪🇹 #humanrightsforall
በነጻ የስልክ መስመራችን 7307 ላይ በመደወል የሰብአዊ መብቶች ጥሰት አቤቱታ ማቅረብ ወይም ጥቆማ መስጠት ይችላሉ።
