
Addis Ababa Education Bureau
May 31, 2025 at 08:54 AM
ለመምህራን ፣ርዕሳነ መምህራን እና ለሱፐርቫይዘሮች የሙያ ብቃት የጽሑፍ ምዘና ተሰጠ።
(ግንቦት 23/2017 ዓ.ም) የጽሑፍ ምዘናው በከተማ አስተዳደሩ በሚገኙ የመንግስትና የግል ትምህርት ቤቶች ለተውጣጡ መምህራን እና የትምህርት ቤት አመራሮች በ10 የምዘና ጣቢያዎች የተሰጠ ሲሆን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ፣ የትምህርትና ስልጠና ቁጥጥር ባለስልጣን እንዲሁም የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር መምህራን ማህበር አመራሮች በዳግማዊ ሚኒሊክ እና ኮከበ ጽበሀ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ተገኝተው የምዘና ሂደቱን ተመልክተዋል።
ምዘናው የተማሪዎችን ውጤትና ስነምግባር በማሻሻል የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ እየተከናወኑ የሚገኙ ተግባራት ውጤታማ እንዲሆኑ የሚያበረክተው አስተዋጽኦ ከፍተኛ መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ዶክተር ዘላለም ሙላቱ ገልጸው የጽሑፍ ምዘና ውጤታማ እንዲሆን ቢሮው ከከተማ አስተዳደሩ የትምህርትና ስልጠና ቁጥጥር ባለስልጣን እና ከመምህራን ማህበር ጋር በጋራ በመሆን በየደረጃው የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራዎችን ከመስራቱ ባሻገር መዛኞችን እና ሱፐርቫይዘሮችን ጨምሮ ምዘናውን የሚያስፈጽሙ ባለሙያዎችን በየምዘና ጣቢያዎች መመደቡን እና ለጽሑፍ ምዘናው የሚያስፈልጉ ግብአቶችን የማሟላት ስራ መስራቱን አመላክተዋል።
የሙያ ብቃት የጽሑፍ ምዘናው መምህራኑ በተመረቁበት የትምህርት አይነት እና የሚያስተምሩበትን የክፍል ደረጃ መሰረት አድርጎ በትምህርት ሚኒስቴር የተዘጋጀ ሲሆን በዛሬው ምዘና ከ9,700 በላይ ለሚሆኑ መምህራን እና የትምህርት አመራሮች በከተማ አስተዳደሩ በተዘጋጁ 10 የምዘና ጣቢያዎች የጽሑፍ ምዘናው መሰጠቱ ተገልጿል።
የጽሑፍ ምዘናው በአማርኛ፣አፋን ኦሮሞ እና እንግሊዘኛ ቋንቋዎች የተሰጠ ሲሆን ለጽሑፍ ምዘናው የተቀመጠውን የማለፊያ ነጥብ የሚያመጡት ተመዛኞች በቀጣይ የማህደረ ተግባር ምዘና እንደሚሰጣቸው ከትምህርትና ስልጠና ቁጥጥር ባለስልጣን የተገኘው መረጃ ያሳያል።
መረጃዎችን በፍጥነት ለማግኘት ማሰፈንጠሪያውን ይጫኑ!
https://linktr.ee/aacaebc

❤️
1